![](https://ethiocab.com/wp-content/uploads/2023/10/ff0a5210-68e5-11ee-909c-0f77bf1c60d8.jpg.webp)
ኢትዮጵያውያኖቹ አትሌቶች ትዕግሥት አሰፋ እና ጉዳፍ ፀጋይን ጨምሮ ሦስት አፍሪካውያን አትሌቶች የዓለም አትሌቲክስ በየዓመቱ ለሚያዘጋጀው የዓለም ምርጥ ሴት አትሌት ሽልማት ታጩ። ከሁለቱ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በተጨማሪ ኬንያዊቷ ፌይዝ ኪፕየጎን በዘንድሮው የዓመቱ የሴቶች የዓለም ምርጥ አትሌት ዕጩ ውስጥ ተካታለች። በአጠቃላይ ለሽልማቱ በዚህ ዓመት አስደናቂ ብቃትን ያሳዩ 11 አትሌቶች ዕጩ ሆነዋል።
ኢትዮጵያዊቷ አትሌት ትዕግሥት አሰፋ ባለፈው መስከረም ወር አጋማሽ ላይ በጀርመኗ በርሊን በተካሄደው 48ኛው የማራቶን ውድድር ክብረ ወሰኑን ከሁለት ደቂቃ በላይ በማሻሻል አሸናፊ ሆናለች። የበርሊን ማራቶን አሸናፊዋ ትዕግስት በርካቶችን ባስደነቀ መልኩ ነበር ሁለት ሰዓት ከ11 ደቂቃ ከ53 ሰከንድ በመግባት የሴቶች ማራቶን ክብረ ወሰን መጨበጥ የቻለችው። ጉዳፍ ፀጋይም ባለበት የአውሮፓውያን ዓመት መስከረም ላይ በአሜሪካዋ ኦሪገን፣ ዩጂን በተካሄደው የዳይመንድ ሊግ የ5 ሺህ ሜትር ውድድር የዓለም ክብረ ወሰንን በማሻሻል አሸናፊ ሆናለች።
የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የ10 ሺህ ሜትር አሸናፊዋ ጉዳፍ ውድድሩን 14 ደቂቃ ከ00.21 በመጨረስ እንዲሁም የውድድሩን ክብረ ወሰን በ5 ሰከንዶች በማሻሻል ድንቅ ብቃትም አሳይታለች ተብሏል። ጉዳፍ ያሻሻለችው ክብረ ወሰን በዘንድሮው ለምርጥ አትሌትነት ዝርዝር ውስጥ በተካተተችው ፌዝ ኪፕየጎን ተይዞ ነበር። የአትሌቲክስ ተንታኞች በዘንድሮው ዓመት ሦስት አዳዲስ የዓለም ክብረ ወሰኖች ማስመዝገብ የቻለችው የ29 ዓመቷ ኬንያዊት ኪፕየጎን አሸናፊ እንድትሆን ድጋፋቸውን እየሰጡ ይገኛሉ።
ኪፕየጎን “በዳይመንድ ሊግ ታሪክ በተለያዩ የውድድር ዘርፎች ክብረ ወሰኖችን መስበር የቻለች እንዲሁም በአንድ የውድድር ዘመን ከአንድ በላይ የዓለም ክብረ ወሰን የሰበረች” ከመሆኗ ጋር ተያይዞ አሸናፊ ልትሆን እንደምትችል ዋንዳ ዳይመንድ ሊግ ዘግቧል። ዜግነቷን ቀይራ ለባህሬን የምትወዳደረው ትውልደ ኬንያዊቷ ዊንፍሬድ ያቪ እንዲሁ በዕጩዎቹ ዝርዝር ውስጥ ገብታለች። ከደጋፊዎች እና ከዓለም አትሌቲክስ ባለሥልጣናት የተሰጡ ድምጾችም ተሰብስበው አሸናፊዎቹ በአውሮፓውያኑ ታኅሣሥ 11/2023 ይፋ ይሆናሉ።
ኢትዮ ካብ ስለሚሰጠው አገልግሎት ለማወቅ ድህረገጻችንን www.ethiocab.com ይጎብኙ
የ Driver application ለማውረድ http://driver.ethiocab.com እንዲሁም የ Customer application ለማውረድ http://user.ethiocab.com