9 መስከረም 2023
በተለይ የትዊተር አዘውታሪዎች ‘ያ ወፍ የሚቀርፀው ሰውዬ’ በሚል መጠሪያ ያውቁታል።አስራት አያሌው ፎቶ አንሺ ነው። 42 ዓመት ሞልቶታል።‘የነፍሱን ጥሪ’ ያገኘው በቅርቡ ነው።ፎቶ ማንሳት ወይ የተማረው ወይ ለዓመታት የቆየበት ሙያ አይደለም። በአጋጣሚ ነው የገባበት።ትምህርቱም፣ የቀድሞ ሥራውም ከፎቶግራፍ ጋር አይገናኙም። በሶሲዮሎጂ ተመርቆ መንግሥታዊ ባልሆኑ ተቋማት ሠርቷል። እርግጥ ከልጅነቱ ጀምሮ ፎቶ ማንሳት ጊዜ ማሳለፊያው፣ መደሰቻው ነበር። ተፈጥሮ ይወዳል። ጸጥ ወዳለ ቦታ መጓዝ ያዘወትራል። ያገኘውን ፎቶ ማንሳት ልማዱ ነው። ከዩኒቨርስቲ ወጥቶ ለመጀመሪያ ጊዜ ገቢ ሲያገኝ የገዛው ካሜራ እንደነበር ያስታውሳል። ፎቶ ማንሳትን ሙያው እንደሚያደርገው ግን አላሰበም። የሕይወት አቅጣጫው የተለወጠው የዛሬ ስምንት ዓመት ገደማ ከባለቤቱ ጋር ከአዲስ አበባ ወደ ባሕር ዳር ሲያቀኑ ነበር። በባሕር ዳር ተፈጥሮ ለመማረክ ጊዜ አልወሰደበትም። ጣና ሐይቅን፣ ዓባይ ወንዝን ፎቶ ያነሳ፣ ቪድዮ ይቀርጽ ጀመር። ከተማዋን “ያልተዋወቀች” ሆና እንዳገኛት ይናገራል። እናም ፎቶዎቹን ትዊተር ላይ እየለጠፈ ከተማዋን ያስተዋውቅ ጀመር። በዚህ መሀል ነው ብዙ አይቷቸው የማያውቅ የአእዋፍ ዝርያዎችን ያስተዋለው።“ጨርሶ አይቻቸው የማላውቅ ነበሩ” ይላል አስራት። ስለ አእዋፉ የበለጠ ለማወቅ መረጃ ሲያስስ በባሕር ዳር ዩኒቨርስቲ መምህር የተዘጋጀ መጽሐፍ አገኘ። መጽሐፉ ዕውቀት ያስጨብጣል። ግን በመጽሐፉ የተካተቱት ፎቶዎች አእዋፉ በአካል ሲታዩ ያላቸውን ገጽታ የሚወክሉ ሆነው አላገኛቸውም። ከሩቅ የተነሱ፣ የደበዘዙ፣ የጠቆሩ ናቸው። አስራት ተፈጥሮንም ፎቶግራፍንም እንደሚወድ ሰው የተሻሉ ፎቶዎች ለማንሳት ወሰነ። “ሁለት ዓመትም ይፍጅ ሦስት በባሕር ዳር ዙርያ ያሉ አእዋፍን ፎቶዎች ላሰባስብ ብዬ ወሰንኩ” ይላል።
ዛሬ ስብስቡ 265 ዝርያዎች ደርሷል። አእዋፉ በባሕር ዳርና በዙሪያዋ የሚኖሩ ናቸው። በአጋጣሚ የገባበትን ሙያ በተለይም ባለፉት ሁለት መታት አጥብቆ ይዞታል።የሙሉ ጊዜ ሥራው ባሕር ዳርና አካባቢው ያሉ አእዋፍን ፎቶ ማንሳት ነው።በእግሩ አልያም በሳይክል እየተዘዋወረ ፎቶ ያነሳል። የአእዋፉን ስም፣ ባህሪ፣ አኗኗርና ሌላም መረጃ የያዘ መጽሐፍ እያገባደደ እንደሆነ ይናገራል። የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ እና የሰሜን ኢትዮጵያው ጦርነት ከፈጠረው ድባቴ እፎይታ ማግኛ መንገዱም ነበር ፎቶ ማንሳት። ኋላ ላይ ግን ደስ ወደሚለው ሙያ ጠቅልሎ መግባትና አንዳች አስተዋጽኦ ማበርከት ወደደ።ይህ ሽግግር “ቀላል አልነበረም” ይላል አስራት።ደመወዝ የሚያስገኝ ሥራን በዚህ ዘመን እርግፍ አድርጎ መተው ቀላል ውሳኔ ሊሆን አይችልም።“መጀመሪያ ላይ ምንም ገቢ ስለማያስገኝ አስቸጋሪ ነበር” ይላል። ሌሎች ባለሙያዎችም በኢትዮጵያ ለአእዋፍ ፎቶ ፍላጎቱ ስለሌለ ሥራው መተዳደሪያ እንደማይሆን ያምኑ ነበር። አሁን ግን ፎቶዎቹን በመሸጥ ገቢ ማግኘት ጀምሯል። “ትልቅ ገቢ ባይገኝም መተዳደሪያ ይሆናል” ይላል። ጎጃም ነው ያደገው። አባቱ የአንደኛ ደረጃ መምህር ኋላ ላይም ርዕሰ መምህር ነበሩ። በየሦስት፣ አራት ዓመቱ ቤተሰቡ የሚኖርበትን አካባቢ ይቀይር እንደነበር ያስታውሳል።አስተዳደጉም ከአእዋፍ ጋር የተገናኘ እንደነበር ያወሳል። አንዱ ወደ ሙያው ለመግባቱ ምክንያቱ አስተዳደጉ ሳይሆን አልቀረም።ባሕር ዳር የውብ አእዋፍ መኖሪያ መሆኗም ሳይጠቀስ አይታለፍም። እሱ ብቻ አይቶ ውበታቸውን ከሚያጣጥም ከብዙኃኑ ጋር መጋራትን መርጧል። መጽሐፉ አእዋፉን “በአይን እንደማየት ያህል ከነሙሉ ውበታቸው” የሚያሳይ እንደሚሆን ያወሳል። ፎቶዎቹን ያለ አንዳች ስስት ትዊተር ገጹ ላይ በማጋራት አስራት ይታወቃል። ሁሉም ነገር ለገበያ በሚቀርብበት ዘመን ለምን ይሆን ፎቶዎቹን በየቀኑ በነጻ ለማጋራት የመረጠው?ፎቶ ስላነሳኋቸው ነው እንጂ ለሁላችንም የተሰጡ የተፈጥሮ ፀጋ ናቸው። መታየት አለባቸው። ምርጥ የምላቸውን ደብቄ በነጻ የምለቀው ሁለተኛ ሦስተኛውን ሳይሆን በጣም ቆንጆ የሆነውን መርጬ ነው የምለቀው። ሁሉም ሰው አይቷቸው ቢደሰት የኔም ደስታ ነው።”
ነጻነትእና አእዋፍ
አእዋፍን ከነጻነት፣ ከሰላም፣ ከወሰን አልባነት፣ ከሙዚቃ ጋር የሚያስተሳስሩ አሉ።አስራት ድንበር የማይገድባቸው ፍጡሮች ይላቸዋል። ከአላስካም ይሁን ከአንታርክቲካ በርረው በየዓመቱ አፍሪካ ይደርሳሉ። ቀዝቃዛውን ጊዜ አሳልፈው ቤታቸው ይመለሳሉ።“የነጻነት ተምሳሌት ናቸው። እንደፈለጉ ቦታ ሳይገድባቸው ይኖራሉ” ሲል ይገልጻቸዋል። ከአብሮነት ጋርም ያስተሳስራቸዋል። ከዓመት ዓመት ጣና የሚኖሩ አእዋፍን ምሳሌ ያደርጋል። አካባቢው ውሃማ፣ ረግረግ ነው። የጣናዎቹ አእዋፍ ከአላስካ ከመጡት ጋር አብረው ተፈጥሮ የሰጣቸውን ሃብት ይጋራሉ።‘የኔ’ ወይም ‘መጤ’ አእዋፍ ጋር አለመኖሩ ነው አስራትን የሚማርከው።“የእኩልነት ተምሳሌቶች፣ የተፈጥሮ ድንቅ ስጦታዎች ናቸው። ከዚህ በላይ ልገልጻቸው አልችልም” ይላል። መልካቸው፣ ባህሪያቸው ያስደንቀዋል።“የአንድ ወፍ ቆንጆ ፎቶግራፍ ሳገኝ የሚሰማኝን ስሜት ልገልጽልሽ አልችልም” ይላል።ሥራው ቀላል ሆኖ አይደለም። በየቀኑ ማልዶ መውጣት፣ ዘለግ ላለ ሰዓት መጠበቅ፣ መመላለስም ያስፈልጋል።“መፈለግ ይጠይቃል። የፈለጉት ደግሞ ቶሎ አይገኝም። ተገኝቶም ቆንጆ ፎቶ ማግኘት ድካም ይጠይቃል። ትልቅ ትዕግስትም የሚጠይቅ ነው። ግን ቆንጆ ፎቶ ያንን ሁሉ ድካም የሚያስረሳ ደስታ ይሰጣል።”ሂደቱንም ውጤቱንም ይወደዋል። ድካሙንም ሳይቀር። ሁልም ስለወፎች ሲነሳ አብሯቸው ሊነሳየሚችለው ሰላም ነው ፡፡ ኢትዮ ካብም አዲሱ አመት የሰላም የፍቅር እንዲሁም የመተሳሰብ እንዲሆንልን ይመኛል ፡፡
ኢትዮ ካብ ስለሚሰጠው አገልግሎት ለማወቅ ድህረገፃችንን www.ethiocab.com ይጎብኙ
የ Customer application ለማውረድ http://user.ethiocab.com እንዲሁም
የ Driver application ለማውረድ http://driver.ethiocab.com ያገኙናል